የኢየሱስ ክርስቶስ

የምስራች

በ5 ቀላል ደረጃዎች

1

መንግሰተ ሰማይ ነፃ ስጦታ ነው።
በዋጋ የምናገኘው ወይንም ከስራችን የተነሳ የሚገባን አይደለም።

*

በልደት ቀንህ ላይ አሁን ጠዋት ነው ብለህ አስብ። እናትህ ውድ በሆነ ስጦታ ሰርፕራይዝ አደረገችህ፟፤ በቅርብ ጊዜ በወጣው አይፎን ስልክ። “ዋው! አመሰግናለሁ እማ!” አልካት። ከዛ እናትህን ለመክፈል ብር ፍለጋ እጅህን ወደኪስህ ከተትክ። ብትከፍልበት ስጦታ ይሆናል? አይሆንም። በዛ ላይ እናትህን ለመክፈል መሞከር በራሱ እንደስድብ ይቆጠራል።

ወይም እንበልና አንድ አባት ወጣት ልጁ በትምህርት ቤት ጥሩ ውጤት እንድታመጣ ለማበረታታት ፈልጎ እንዲህ አላት “በዚህ አመት ሁሉንም ትምህርቶች A ካመጣሽ ፤ ለገና መኪና እገዛልሻለሁ።”

በዓመቱ መጨረሻ ሁሉንም ትምህርቶች A አገኘች፤ አባትም ቃሉን ጠብቆ መኪና ገዛላት። ታዲያ ይሄ ስጦታ ነው? በጭራሽ አይደለም፣ ይልቁንስ ለስራዋ የሚገባ ሽልማት እንጂ።

ስጦታ በነፃ የሚሰጥ በነፃም የሚቀበል መሆን አለበት። ስጦታውን ለማግኘት መክፈል ካለብህ፣ ወይንም ማድረግ ያለብህ ነገር ካለ ያ በፍፁም ስጦታ አይሆንም።

መፅሃፍ ቅዱስ መንግስተ፟፟-ሰማይ (ዘላለማዊ ህይወት) ነፃ ስጦታ እንደሆነ ይነግረናል።

ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም።

ወደ ኤፌሶን ሰዎች 2:8-9

የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘላለም ሕይወት ነው።

ወደ ሮሜ ሰዎች 6፡23

በመንግስተ-ሰማይ ማንም ስፍራ አይገባውም። ማንም ደግሞ በመንግተ-ሰማይ ስፍራን በገንዘቡ ወይም ባደረጋቸው መልካም ስራዎች ብዛት ሊያገኝ አይችልም።

ይሄ የሆነበት ምክንያት…

2

ሰው ሃጢያተኛ ነው።
ራሱን ማዳን አይችልም።

*

በስድስት እንቁላል የሚሰራ ኦምሌት እየሰራሁ ነው ብለህ አስብ። አንድ በአንድ እያንዳንዱን እንቁላል እየሰበርክ አስኳሉን ወደ መምቻ ሳህኑ አስገባህ። የመጨረሻውን እንቁላል ልትሰብር ነው፣ ሰበርከው ወደ መምቻ ሳህንህ ውስጥም አስገባኽው። በድንገት ጭንቅላትህን አዙረህ አፍንጫህን ያዝክ። ለካስ የመጨረሻው እንቁላል የተበላሸ ነው።

ሁሉንም ከመጣል ውጪ ሌላ አማራጭ የለህም። በሳህኑ ውስጥ አምስት ጤነኛ እንቁላሎች ቢኖሩም እንኳ አንዱ የተበላሸው እንቁላል ሁሉንም ይበክላል።

ልክ አንተ ለቤተሰብህ በአንድ የተበላሸ እንቁላል የተበከለን ኦምሌት ለምግብነት እንደማታቀርብ ሁሉ ቅዱስ ለሆነውም ለእግዚአብሄር በአንድም ሃጢያት እንኳን ቢሆን የተበከለን ህይወት እያቀረብን እርሱ እንዲቀበለን መጠበቅ የለብንም።

የእግዚአብሄር ደረጃ እጅግ ከፍ ያለ ነው። ለእርሱ፣ ቁጣ ነፍስን እንደመግደል ነው፤ የስጋዊ ምኞት ሃሳብ እንደማመንዘር ነው። ሃጢያት የምናደርገው ነገር ብቻ አይደለም ነገር ግን ማንኛውም የምናስበው፣ የምንናገረው፣ የምናደርገው እንዲሁም ከእግዚአብሄር ፍፁም ደረጃ አንፃር የማናደርጋቸው ወይም ያላደረግናቸውን ነገሮችንም ያጠቃልላል።

ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል

ወደ ሮሜ ሰዎች 3፡23

እንዲህ ብለህ ታስብ ይሆናል “ግን እኮ ጥሩ ሰው ነኝ”፣ “ለቤተሰቤ አስባለሁ”፣ በማህረሰቤ ውስጥ በፈቃደኝነት አገልግሎት እሰጣለሁ” ፣ “አልሰርቅም ወይም ማንንም አልጎዳም”፣ “በእርግጥ ወደ መንግስተ ሰማይ መግባት አለብኝ”

መልካም ህይወት ለመኖር እየተጣጣርክ መንግስተ-ሰማይ ለመግባት ከፈለክ ኢየሱስ ይሄን ያክል መልካም መሆን አለብህ ብሏል፡

እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ።

የማቴዎስ ወንጌል 5፡48

ወደ መንግስተ፟- ሰማይ መግቢያ መስፈርቱ ፍፁም የሆነ ሃሳብና ስራ ነው። በአጭሩ እንደ እግዚአብሄር ፍፁም መሆን አለበህ። ይሄ ደግሞ የሰው ልጅ ሊደርስበት የማይችል ደረጃ ነው።

ደግሞም መልካም ስራዎች ሊያድኑን አይችሉም ምክንያቱም...

3

እግዚአብሄር አፍቃሪም ፃድቅ ፈራጅም ነው።

*

አንድ በጣም የተቸገረ ሰው ባንክ ሊዘርፍ ወሰነ ብለህ በምናብህ አስብ። ወደገንዘብ ተቀባይዋ ቀረበ ከዚያም ሽጉጡን ደቅኖባት እየጮኽ ገንዘብ እንድትሰጥው ያስገድዳታል።

በሁኔታው የተደናገጠችው ገንዘብ ተቀባይ ብሩን ትሰጠዋለች።

በፍጥነት ብሩን በያዘው ላስቲክ ውስጥ አጭቆ ወደ መውጫ በሩ ይገሰግሳል። ነገር ግን በመንገዱ ላይ ምንጣፉ አደናቅፎት በቁመቱ ወደቀ ሽጉጡንም ጣለ። የባንኩ የጥበቃ ስራተኞችም ወዲያውኑ ያዙት።

ፍርድ ቤት ውስጥ ሳለ ዳኛው ሌባውን እንዲህ ብሎ ጠየቀው፡ “እንዴት ብለህ ይግባኝ ትጠይቃለህ?”

“ጥፋተኛ ነኝ” ብሎ መለሰ በዝግታ ድምፅ። ሌላ አማራጭ አልነበረውም። የተገኘበት ማስረጃ እጅግ ብዙ ነበር።

“ክቡር ዳኛ” ሌባው ንግግሩን ቀጠለ “ጥፋቴ ይሄ ነው። ማንንም አልጎዳሁም። ባንኩም ቢሆን ገንዘቡ ተመልሶለታል። እባክዎን የሰራሁትን ሁሉ ረስተው ሊለቁኝ ይችላሉ?”

ዳኛው ሌባውን ቢለቀው ፃድቅ(ትክክለኛ) ይሆናል? አይሆንም። ዳኛው ህጉን ማስከበር አለበት ህጉ ደግሞ ሲሰርቅ የተገኘ ሰው ተገቢውን ቅጣት እንዲቀበል ያስገድዳል።

እግዚአብሄር ከየትኛውም የሰው ዳኛ ይልቅ ፃድቅ ነው። እርሱ ኃጢያታችንን በቀላሉ ሊያልፈው አይችልም፣ አያልፈውምም።

… እግዚአብሔር ፍቅር ነው።

1ኛ የዮሐንስ መልእክት 4፡8

እስከ ሺህ ትውልድም ቸርነትን የሚጠብቅ፥ አበሳንና መተላለፍን ኃጢአትንም ይቅር የሚል፥ በደለኛውንም ከቶ የማያነጻ፥ የአባቶችንም ኃጢአት በልጆች እስከ ሦስትና እስከ አራት ትውልድም በልጅ ልጆች የሚያመጣ አምላክ ነው ሲል አወጀ።

ኦሪት ዘጸአት 34፡7

ግራ መጋባቱ እዚህ ጋር ነው። እግዚአብሄር ፍቅር ነው ስለዚህ ሊቀጣን አይፈልግም ነገር ግን ደግሞ ፃድቅ ፈራጅም ነውና ሃጢያታችንን መቅጣት ይኖርበታል።

ይሄንን ግራ መጋባት እግዚአብሄር ኢየሱስን ወደዚህ ዓለም በመላክ ፈትቶታል…

4

ኢየሱስ አምላክና ሰው ነው።
ለሃጢያታችን ሁሉ ቅጣትን ተቀብሏል።

*

ኢየሱስ በስጋ(በሰው አምሳያ) የተገለጠው እግዚአብሄር ነው። እርሱ መልካም ሰው፣ ከነቢያቶች አንዱ ወይንም ታላቅ አስተማሪ አልነበረም።

በመጀመሪያ ቃል(ኢየሱስ ክርስቶስ) ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። ቃልም ሥጋ(ሰው) ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተሞልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።

የዮሐንስ ወንጌል 1፡1፣14

እግዚአብሄር እኛን ይወደናል ሃጢያታችንን ግን ይጠላል። ከእኛ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖረው ሁሌም ይናፍቃል ነገር ግን ሃጢያታችን እርሡን ከእኛ የለየው ግንብ ነው።

ይሄንን ችግር ለመፍታት እግዚአብሄር ሃጢያታችንን ሁሉ ወሰደ፤ ያለፉትን ፣ አሁን ያሉትን ደግሞም ወደ ፊትም የምናደርጋቸውን ሃጢያቶች በአጠቃላይ በኢየሱስ ላይ አስቀመጣቸው። ከዚያም እኛ ለሰራናቸው ሃጢያቶች ኢየሱስን ቀጣው።

እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ።

ትንቢተ ኢሳይያስ 53፡6

ኢየሱስን እንዲያዋርዱትና እንዲያሰቃዩት ለአረመኔ ሰዎች አሳልፎ ተሰጠ። በቡጢና በጥፊ ተመትቷል፣ ምራቅ ተተፍቶበታል። በሚገረፍበት ወቅት ስጋው ከላዩ ላይ ተቦጭቆ ተነስቷል። ምክንያቱም መግረፊያ አለንጋዎቻቸው ጫፋቸው እሾሃማ ብረት ነበራቸው።

ሰዎች እያፌዙበት ፣ የእሾህ አክሊል በጭንቅላቱ ላይ በጉልበት ተደረገ። ከዚያም የብረት ሚስማሮች በእጆቹና በእግሮቹ ውስጥ ተቸንክረው በመዶሻ ተመቱ። በመስቀል ላይ ተሰቀለ።

በመጨረሻም ለመጨረሻዋ ሃጢያት ከፍሎ ሲጨርስ ኢየሱስ እንዲህ አለ “ቴሌስታይ” ይሄ ቃል በጥንት ጊዜ በገበያ ላይ የሚጠቀሙት የግብይይት ቃል ሲሆን ትርጉሙም “ዋጋው ተከፍሏል” ማለት ነው።

ኢየሱስ ሞተ ነገር ግን ከሶስት ቀን በኋላ እግዚአብሄር ከሙታን አስነሳው።

ይህ ማለት ሃጢያቶችህ ባጠቃላይ ተቀጥተዋል ማለት ነው፣ ብቸኛ ያልሆነው ነገር ባንተ/ባንቺ ሰውነት ውስጥ አለመቀጣታቸው ነው።

ኢየሱስ የሃጢያታችንን ቅጣት ከመክፈልና ለእኛ በመንግስተ-ሰማይ ስፍራን ለመግዛት በመስቀል ላይ ሞተ ሞትንም ድል አድርጎ ተነሳ። አሁን ይሄንን ስፍራ በስጦታ መልክ ለእኛ በነፃ አቅርቦታል።

ሳሙናን እስካልተጠቀምነው ድረስ ሰውነታችንን ሊያፀዳልን እንደማይችል ሁሉ ይሄ ከእግዚአብሄር የተሰጠን ነፃ ስጦታም በህይወታችን ላይ ሊጠቅመን የሚችለው ስንቀበለው ብቻ ነው።

ይህንን ስጦታ የምንቀበለው በእምነት ነው…

5

የመንግሰተ ሰማይን በር የሚከፍተው ቁልፍ
እምነት ነው።

*

በግድግዳ ላይ የተሰቀለው ክብ የነፍስ አድን መንሳፈፊያ።

ወደ ባንክ አካውንቴ ለመግባት የይለፍ ቃል ማስገባት አለብኝ። ብዙ የተለያዩ የይለፍ ቃሎች ልሞክር እችላለሁ ነገር ግን የሚሰራልኝ ትክክለኛው የይለፍ ቃል ብቻ ነው። ወደ መንግሰተ ሰማይ የሚያስገባው ብቸኛ የይለፍ ቃል የሚያድን እምነት ነው።

የሚያድን እምነት ምንድን ነው?

አንዲት ሳይንቲስት ስለውሃ ብዙ ነገር ልታውቅ ትችላለች ነገር ግን በበረሃ ላይ ጥም ይዟት ብትንከራተት ስለውሃ ያላት እውቀት ብቻውን ሊያድናት አይችልም። የግድ ውሃ መጠጣት አለባት። ልክ እንዲሁ እግዚአብሄር እንዳለ ማወቃችን ብቻ ሊያድነን የሚችል እምነት አይደለም።

ለጉዞ ከመነሳታችን በፊት እግዚአብሄር በመንገዳችን እንዲጠብቀን የአደራ ፀሎት እንፀልይ ይሆናል ወይም ፈተና ከመፈተናችን በፊት በፈተናው ላይ እግዚአብሄር እንዲረዳን እንፀልይ ይሆናል። እርዳታ ስንፈልግ ብቻ ወይም አጣብቂኝ ሁኔታ ውስጥ ስንገባ ብቻ እግዚአብሄርን መፈለግ ዘላቂነት የሌለው ጊዜያዊ እምነት ነው።

የሚያድን እምነት እግዚአብሄር እንዳለ ማወቅ ወይም ወቅታዊ እምነት አይደለም። እውነተኛ የሚያድን እምነት ለዘላለማዊው ህይወት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ማመን ነው።

ወደ ውጭም አውጥቶ፦ ጌቶች ሆይ፥ እድን ዘንድ ምን ማድረግ ይገባኛል? አላቸው።
እነርሱም፦ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እመን አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ አሉት።

የሐዋርያት ሥራ 16:30-31

በታንኳ ላይ ሆነህ ባህሩን እየቀዘፍኩ ነው ብለህ አስብ። በድንገት በብርቱ አውሎ ነፋስ ተያዝክ። ከባድ የባህር ሞገዶች ታንኳህን ሊሰባብሯት በሃይል መጡ ታንኳህንም ሰባበሯት። አንተም በበረዷማ ውሃ ውስጥ በታላቅ ድንጋጤ ተውጠህ በአንዲት ስባሪ እንጨት ላይ ተንጠልጥለህ ቀረህ።

አንድ መርከብ ከሩቅ አይቶህ ወደ አንተ በፍጥነት ለመድረስ በችኮላ መምጣት ጀመረ። ከዚያም የመርከቡ ካፒቴን ወደ መርከቡ ዳር መጥቶ “የህይወት አድን መንሳፈፊያ እወረውርልሃለሁና ያዘው! አይዞህ እንደርስልሃለን” አለህ።

በተመሳሳይ መንገድ እግዚአብሄር በሃጢያታችን ውስጥ ስንሰምጥ አይቶናል። ራሳችንን ለማዳን ሃይል የለንም። ስለዚህም እንዲህ ብሎ ወደ እኛ ይጣራል “የነፍስ አድን መንሳፈፊያውን ወርውሬላችኋለሁ ስሙም ኢየሱስ ይባላል። የያዛችሁትን ስባሪ እንጨት ልቀቁና እኔ የላክሁላችሁን እርሱን ያዙት ያኔ ወደ መርከቤ እስባችኋለሁ”።

አንዱን መምረጥ አለብን - ወይ ስባሪው እንጨት ላይ መንጠላጠል(ራሳችንን በመልካም ስራችን ለማዳን መሞከር) ወይ ደግሞ ስባሪውን እንጨቱን በመልቀቅ ፈፅሞ እንዲያድነን በኢየሱስ ላይ መታመን ።

ወደ ዘላለማዊው ህይወት መግቢያ ብቸኛ መንገድ ኢየሱስ ነው። እርሱ የእግዚአብሄር ብቸኛው የነፍስ አድን መንሳፈፊያ ነው። የዘላለማዊ ህይወት ስጦታን ለመቀበል እምነታችንን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ብቻ ማድረግ አለብን።

ይሄ መልእክት ትርጉም ሰጥቶሃል?

*

ይሄንን ፅሁፍ በአጋጣሚ አይደለም እያነበብክ ያለኽው። እግዚአብሄር ይወድሃል። ለሃጢያቶችህ ሁሉ ስርየትን በማቅረብ ወደቤተሰቡ ሊቀላቅልህ ይፈልጋል።

የዘላለም ህይወት ስጦታን መቀበል ትፈልጋለህ?

ምንም አይነት የግዴታ መከተል ያለብህ የተወሣሠበ ስነ ሥርዓት የለም። ስጦታውን በቀላሉ በመጠየቅ ብቻ ነው የምትቀበለው።

መልስህ አዎን ከሆነ እባክህ ይሄንን ፀሎት አሁን ፀልይ፡

ውድ ኢየሱስ ሆይ፣ እኔ ሃጢያተኛ ነኝ። የዘላለማዊው ህይወት ነፃ ስጦታህን መቀበል እፈልጋለሁ። አንተ የእግዚአብሄር ልጅ እንደሆንክ አምናለሁ። ለሃጢያቶቼም እንደሞትክልኝ አምናለሁ። ከሙታንም እንደተነሳህ አምናለሁ። እምነቴን ባንተ ላይ ብቻ ለማድረግ ወስኛለሁ። ኢየሱስ ሆይ ስለዘላለማዊው ህይወት ነፃ ስጦታህ አመሰግንሃለሁ። አሜን።

አሁን ስላደረከው ነገር ኢየሱስ እንዲህ ብሎ ተናግሯል፡

እውነት እውነት እላችኋለሁ በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።

የዮሐንስ ወንጌል 6፡47

ይህ ማለት ልክ ባመንንበት ቅፅበት ዘላለማዊ ህይወትን ተቀብለናል ማለት ነው። በባመንህ ምክንያት ተቀብለኽዋል።

ለተቀበሉት(ኢየሱስን) ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።

የዮሐንስ ወንጌል 1:12-13

አሁን የእግዚአብሄር ቤተሰብ አንድ አካል ሆነሃል። ምንም የምታደርገው ነገር ይሄንን ሊቀይረው አይችልም፣ አንድ ጊዜ የተወለደ ህጻን ተመልሶ አለመወለድ አይችልም።

ያለፉት ፣ አሁን ያሉት ገና ወደፊትም የሚመጡት ሃጢያቶችህ በሙሉ ይቅር ተብለዋል። በእግዚአብሄር አይኖች ስትታይ ልክ እንደ ኢየሱስ ዛሬም ወደፊትም እንደሚያንጸባርቅ ፀዳል ንጹህ ነህ።

ከእንግዲህ በኋላ የፍርሃት ባሪያ አይደለህም...

በአባቱ ክንድ ላይ ያለው ልጅ

አንተ

የእግዚአብሄር ልጅ ነህ